Saturday, September 24, 2011

ሰላምና መረጋጋት በእሥራት?

በጌቱ ጥበበ
በማንኛውም አካባቢና ማኅበረሰብ የተረጋጋ ኑሮ ለመኖር ሰላም፣ጸጥታ፣መረጋጋትና ስምምነት ከምንም በላይ ቅድሚያ የሚሰጣቸው አስፈላጊ ነገሮች ናቸው:: ዓለማችን የተለያየ እምነት፣ ባህል፣ አመለካከትና የአኗኗር ዘዴ ያላቸው ነገር ግን ተፈጥሮ ተመሳሳይ ሰብአዊ ባሕርይ ፍላጎትና የኑሮ ዓላማ የለገሰቻቸው ሕዝብ የሚኖሩባት የብዙዎች መኖሪያ የብዙዎች ማደሪያ ናት:: ሰዎች የሚለያዩባቸውን እምነቶች ባህሎች አመለካከቶችና ልማዶች እርስ በርሳቸው ሳይጋጩ ራሳቸውን ችለው እንዲሄዱ በማድረግ ተስማምተውና ተከባብረው መኖር ከቻሉ ዓለም የሰዎችን መሠረታዊ ፍላጎቶች በሚገባ ሊያሟሉ የሚችሉ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ግብዓቶች አሏት:: በተቃራኒው ልዩነቶቻቸውን መሠረት አድርገው የየራሳቸውን ቡድንና ጎራ በማደራጀት እርስ በርሳቸው የሚተነኳኮሉ ከሆነ ግን የሽብር የሁከትና የእልቂት መድረክ ከመሆን በቀር በምንም መንገድ እንኳን ለሰብአዊ ፍጥረት ለእንስሳትና ለአራዊትም መኖሪያነት ምቹና ብቁ ልትሆን አትችልም::

አሳቡን ጠበብ አድርገን በሀገር ደረጃ ስንመለከተው ሀገር የዓለም አንድ አካል እንደመሆኗ መጠን ስለዓለም የተናገርነው ሁሉ ሀገርንም ይመለከታል:: ማንኛዋም ሀገር ሉዓላዊነቷ ተጠብቆ ህልውናዋ እንዲቀጥል ብሎም ለምታና አድጋ ለዜጎቿ የምታበረክተው ተፈጥሮአዊ ገጸ በረከት ከጊዜ ወደ ጊዜ በዝቶና ተትረፍርፎ ሥጋዊና መንፈሳዊ ርካታን የሚያጎናጽፍ እንዲሆን ከወርቅና ከነዳጅ ክምችት ይልቅ የሚያስፈልጋት አንፃራዊ ሰላም ነው:: ለሰላም መስፈን ደግሞ የዜጎች መቻቻል መከባበርና መስማማት ወሳኝ ጉዳይ ነው:: ዜጎች ስንልም በርእሰ ብሔርነት ወንበር ከተቀመጠው የሀገር መሪ በመንገድ ዳር ላስቲክ ለብሶ እስከሚያድረው ጎዳና ተዳዳሪ ድረስ ማለታችን ነው:: ሁሉም የልዩነት ምክንያት የሆኑ ነገሮችን ወደጎን በመተው መደማመጥና ማመን ማሰመን ባለበት ምክክርና ውይይት በጋራ ፍላጎት ዓላማና ግብ ለመስማማት መጣር ይኖርባቸዋል:: ስምምነቱም ሁሉንም ወገን የሚያካትት ሰላም በሰፈነባት ሀገር ሰላማዊ ኑሮ ለመኖር ከመሻት የመነጨ መሆን አለበት:: በተለይ ሕዝቦችን ለመምራትና ለማስተዳደር በኃይልም ይሁን በሕዝብ ፍላጎት በመሪነት ቦታ የተቀመጡት የሀገር ሰላምና ህልውና መሠረት ለሆነው ብሔራዊ ስምምነትና አንድነት መረጋገጥ ከፍተኛውን ሚና መጫወት ይጠበቅባቸዋል:: በዚህ ዙርያ ጥያቄ የሚነሣ አይመስለኝም አጠያያቂውና አከራካሪው አንዳንዴም በስምምነት ፈንታ ጠብን በአንድነት ፈንታ ልዩነትን በመረጋጋት ፈንታ ሁከትን የሚያስከትል ግዙፍ ችግር ሆኖ ለሀገር መታመስና ለዜጎች መጎዳት መንሥኤ የሚሆነው መሪዎች ሰላምንና መረጋጋትን እናሰፍናለን ብለው የሚከተሉት ትክክለኛ ያልሆነ አመለካከት ወይም ፖሊሲ ነው::

ከብዙ ሀገሮች ልምድ እያየነው እንዳለው ሰላምን ለማስፈን የተሻለው አማራጭ የኃይል ርምጃ መውሰድ ነው ብለው የሚያምኑ መሪዎች ብዙ ናቸው:: በሀገራችንም በገሀድ እየተንፀባረቀ ያለው ይኸው ነው ማሠር ማንገላታት ማሳደድ ማፈናቀል ማስፈራራት:: በርግጥ ይህን የመሰለው የኃይል ርምጃ ሰላምና መረጋጋትን ያመጣል ወይ ብለን ራሳችንን ስንጠይቅ ግን ሐቁን ሌላ ሆኖ እናገኘዋለን: ሰላም ቢደፈርስ ሁከት ቢነሣ መረጋጋት ቢጠፋ የተናጋ ሰላምን መልሶ ለማስፈን መረጋጋትን ለማምጣት የተሻለው አማራጭ በግልጽ ውይይት አምኖና አሳምኖ ቅሬታን ማስወግድና የችግሩን መንሥኤዎች አጥንቶ መፍትሔ መፈለግ ነው እንጂ ዜጎችን በጅምላ ማስፈራራትና ከሕዝብ ጎን ቆመው ለሕዝብ የሚከራከሩ የሕዝብ እንደራሴዎችን ማሠርና ማንገላታት መቼም ቢሆን ሰላምን አምጥቶ አያውቅም ሊያመጣም አይችልም:: የኃይል ርምጃ የሰላም ምንጭ ቢሆን ኖሮ በሰላማዊ ዜጎች ላይ በአይሮፕላን ቦንብ ያስጣለ ጋዳፊ ለ42 ዓመታት የተንደላቀቀበትን ሥልጣን ባላጣ ስደተኛም ባልሆነ ነበር:: አሠረ ገረፈ ገደለ ቦንብ ጣለ መትረየስ ተኮሰ ነገር ግን ይህ ሁሉ ተቃውሞውን ይበልጥ የሚያቀጣጥል ቤንዚን ሆነና ለራሱና ለቤተሰቦቹ ጥፋት ምክንያት ሆነ ገና የሚጠብቀውንስ ማን ዐወቀው?

ሌላው አሳዛኝ ነገር መሪዎች ከሌሎች መሪዎች ገጠመኝ መማር አለመቻላቸው ነው:: የኃይል ርምጃ ለዚያውም በሕዝብ ላይ ውድቀትን እንጂ መልካም ውጤት እንዳላመጣ ከሙባረክና ከጋዳፊ አሳፋሪ ውድቀት አይተው እንደ ብልህ መሪ ለአፍታ ቆም ብለው ራሳቸውንና ፖሊሲያቸውን በመፈተሽ ተመሳሳይ ጥያቄ ሳይነሣ ለሕዝቤ መልስ ልስጥ ብሎ የሕዝቡን ልብ ትርታ አዳምጦ ማሻሻያዎችን በማድረግ ፈንታ በተመሳሳይ ሁኔታ ጉልበታቸውን በሰላማዊ ዜጋ ላይ ባማሳየት የሕዝብን ጥያቄ በኃይል አፍኖ ለማስቀረት የሚጣጣሩ መሪዎችን እያየን ነው:: ከእነዚህም መካከል የሀገራችን መሪዎች ግንባር ቀደም ተጠቃሾች ናቸው:: ገና ለገና የኢትዮጵያ ሕዝብ በሥርዓቱ ደስተኛ ስላልሆነ ገነ ከነገ ወዲያ ሆ ብሎ ሊነሣብን ይችላል ብለው በመሥጋት ርምጃ እንወስዳለን ጣት እንቆርጣለን ብሎ በሚዲያ ከማስፈራራት ባለፈ ሕዝብ ይሰማቸዋል ብለው የሚገምቷቸውን የምስኪኑ ሕዝብ ተከራካሪዎች የሆኑ ጋዜጠኞችንና የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችን ወህኒ አውርደው እነርሱ የተንደላቀቀ ኑሯቸውን ቀጥለዋል:: ምናልባት ይህን ማድረጋቸው ሕዝቡ ፈርቶ ጸጥ ብሎ እንዲገዛ ያስችላል ብለው ሊያስቡ እንደሚችሉ ግልጽ ነው:: እዚህ ላይ አንድ ያላስተዋሉት ነገር ያለ ይመስለኛል በአሸባሪነት ጠረጠርናቸው ብለው ያሠሯቸው ሰማኒያና መቶ ሰዎች ብቻ አይደሉም በመንግሥት አመራር የተማረሩት፡ የከፋቸው ያዘኑት መግቢያ መውጫው ጠፍቷቸው የተጨነቁት ሚልዮኖች ናቸው የሥርዓቱ ተጠቃሚዎች ከሆኑ ጥቂቶች በስተቀር መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው:፡ ከፋኝ ኑሮ ከበደኝ ፍትሕ ተጓደለብኝ ሰሚ አጣሁኝ እያለ በኃዘን የሚኖር 80 ሚልዮን ሕዝብ ከፋው ሆድ ባሰው እያሉ የሚጮሁለት ሰዎች ስለታሠሩ ለችግሬ መፍትሔ አገኘሁ ብሎ ዝም ብሎ ይቀመጣል ብሎ መገመት ሞኝት ነው:፡

በርግጥ ለጊዜው ዛቻውንና በታሣሪዎች ላይ የሚደርሰውን አካላዊና አእምሮአዊ ጉዳት ያዩ ከሩጫቸው ጋብ ሊሉ ይችላሉ ግን ይህስ ቢሆን እስከመቼ ይቀጥላል አዎን ሊሆን አይችልም በዙሃኑ በኖሮ ተጎሳቁለው የጥቂቶች በላተኞች ተመልካች ሆነው የኖሩበት ዘመን ብዛት ከዚህ በኋላ ምንም ዓይነት የኃይል ርምጃ ቢወሰድ አሜን ብሎ ከከፋ ችግርና በደል ጋር እንደገና አብሮ ለመኖር እሺ የሚል ስሜት ከቶ አያመጣም:: አህያ ጅብን የምትፈራው በሩቅ ስታየው ወይም ድምፁን ስትሰማ ነው መቅረቡን ስታይና ልትበላ መሆኗን ስትረዳ ግን ባለ በሌለ ኃይሏ በጥርሷ ነክሳ ትታገላለች እናም ይሳካላታል በላተኛውን ትጥላለች:: በየዋህነት ያሉትን አድርጎ ያሉትን ሆኖ ሲገዛ የኖረውም ሕዝብ ምሬቱ ጫፍ የደረሰ ቀን ገንፍሎ ሲነሣ ምንም ዓይነት ኃይል ቢሰለፍ የሚያቆመው አይሆንም:: ይህ አሁን መሪዎች ሰላማዊ ትግልን እንደ አሸባሪነት በመቁጠር በሕዝብ ላይ ፍራቻና ስጋት ለማሳደር የሕዝቡን አካላት በሰበብ በአስባቡ አሥሮ ማሠቃየት ወደዚሁ አላስፈላጊ ሁከት እንዲገባ ሕዝብን የሚገፋፋ ተግባር ነው እንደውም አሸባሪነት ሊባል የሚችለው ይህ ነው ምስኪኑ ሕዝብ እየራበውም ቢሆን ሀገር ሰላም ብሎ እንዳይኖር ቀጣዩ ታሣሪ ማን ይሆን እኔ ወይስ ልጄ ወንድሜ እህቴ? ነገ ምን እንባል ይሆን ምን ያደርጉን ይሆን? እያለ በስጋትና በሰቀቀን እንዲኖር ማድረግ::

ይህ በርግጥም ቀላል ግምት የሚሰጠው አደጋ አይደለም የኅብረተሰብ ስነ ልቦና ሲጎዳ የምትጎዳው ሀገርም ጭምር ናት ምክንያቱም ሕዝብ የስነ ልቡና ጉዳት ሲደርስበት በተስፋና በፈቃደኝነት ሠርቶ ውጤታማ ሊሆን አይችልም ሥራና ውጤት ከሌለ ደግሞ ሳታጣ ያጣች ይህ አሳዛኝ ሀገር ነገዋ ከትናንት የከፋ ይሆንና ከሀገርነት ደረጃ ልትወጣ ትችላለች ማለት ነው:: ታዲያ መሪዎች ሕዝብን ሊያገለግሉበት በያዙት ሥልጣን ተጠቅመው በሕዝብ ላይ ጉልበታቸውን ለማሳየት ሲሞክሩ ይህን አስበውት ይሆን? በእኔ እምነት የታሠሩት ጥቂት ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ሀገርም ናት ምክንያቱም ሕዝብ በሁከትና በግርግር ምክንያት ሠርቶ አምርቶ ውጤታማ ምርታማ እስካልሆነ ድረስ ሀገር ልትለማና ልታድግ ሕዝብ እየታወከ እየተጨነቀ ሀገር ሰላምና መረጋጋትን ልታገኝ አትችልምና::

ድር ቢያብር አንበሳ ያስር!

በጌቱ ጥበበ

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች መካከል- በተለይም ከኢትዮጵያ ውጪ ባሉቱ- እያየነው ያለው የትብብር መድረክ የወያኔ/ኢሕአዴግን አገዛዝ ለመጣል በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ነው። ከዚህ ቀደም ብዙም ያልተሠራበት ይህ ዓይነቱ የትብብር መድረክ ለውጥን ለማምጣት ካለው አዎንታዊ አስትዋጽዖ ባሻገር ከለውጥ በኃላ መመሥረት አለበት ለምንለው ሥርዓት ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው አከራካሪ አይደለም።
የወያኔ አገዛዝ ሥልጣን ከያዘ ጊዜ ጀምሮ ሕዝቡን ዘርን በተለይም ቋንቋን መሠረት በማድረግ ለመከፋፈል እና በአንድነት ሊመጡበት የሚችሉትን ተቃውሞዎች ለማዳከም የተከተለው መንገድ የሥልጣን እርፉን እንደያዘ እንዲቀጥልና ሊደርስብኝ ይችላል ብሎ ካሰበው ተቃውሞ በተወሰነም ደረጃ ቢሆን ሊታደገው ችሏል።  ይህንንም ለማድረግ ያስችለው ዘንድ በሌሎች ሀገራት ላይ ተሞክሮ በአንድ ሀገር ሕዝብ መካከል ግጭትን ለማስወገድ ይሄነው የሚባል ውጤት ያላሳየውን ይልቁንም ለርስ-በርስ ግጭት ምክንያት የሆነውን በዘር/ቋንቋ ላይ መሠረተ ያደረገ የፌዴራል  ሥርዓት በመዘርጋትና የኢትዮጵያን ታሪክ አንድነትን ሊያዳክም፣ በሕዝብ መካከል ጥላቻን እና ጠብን ሊፈጥር በሚችል መልኩ እንደገና በመጻፍና በመተረክ  የከፋፍለህ ግዛ ዓላማውን ለማሳካት ሞክሮዋል። ላለፉት 20 ዓመታትም ሙሉ በሙሉም ባይሆን በተወሰነ ደረጃ የዚህ ዓላማውን ግብ ሊያሳካ ችሏል። በሕዝብም መካከል መፈራራትን እና ርስ-በርስ መከባበርንና አመኔታ ማጣትን ፈጥሯል።  ይህም ያንድነትን ትግል ማዳከሙ የማይካድ ያደባባይ ሐቅ ነው።

ይህ ሆኖ ሳለ በነኝህ ባለፉት ዓመታትም ብዙዎቹ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ድርጅቶች ዋነኛ ትኩረታቸው አድርገው ይሠሩ የነበረው አሁን በሥልጣን ላይ ያለውን አገዛዝ በማስወገድ ላይ የነበረ መሆኑ ግልጽ ነው። በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ተቀራርቦ ለመሥራት ንግግር የነበረ ቢሆንም ውጤታማ ሆኖ አላየነውም። ይህ ሊሆን የቻለበት ዋነኛው ምክንያት የድርጅቶቹ የመነጋገርያ ርዕሰ ጉዳይ ወያኔን እንዴት እንጣለው እንጂ ከዛ በኃላ የሚኖረው ሥርዓት ምን መምሰል አለበት በሚለው ላይ አለማተኮሩ ነው። 

ምንም እንኳን ያንድነት ትግሉ ወያኔን ለማስወገድ ትልቅ ቦታ ቢኖረውም ትግሉን በጽኑ መሠረት ላይ ለመጣልና በዋነኝነት ለትግሉ ስኬታማነት እንቅፋት የሆነውን የመፈራራት እና ያለመተማመንን ጉዳይ ለማስውገድ ከወያኔ ውድቀት ወድያ ስለምትገነባው የዜግነት እኩልነት፤ የሰብአዊ፣ የፖለቲካዊና የኤኮኖሚ መብቶች የሚጠበቁባት፣ ሁሉንም ግለሰብም ሆነ ቡድን በእኩል የሚያስተናግድ የፍትህ ሥርዓት የሰፈነባት ኢትዮጵያን ለመፍጠር ንግግር፣ ምክክር፣ ውይይት ምርጫ የሌለው ጎዳና ነው። ይህ ዓይነቱ የበሰለ አካሄድ ከለውጥ በኃላ ሊያጋጥሙ የሚችሉ የርስ-በርስ ግጭቶችን ከማስቀረት አኳያ ትልቅ ቦታ ይኖረዋል። ለዚህም ሲባል ነው ይህ ሰሞኑን እያየነው ያለው የውይይት መድረክ ዓይነቶች ጠንክረው መሠራት አለባቸው፣ ተበራክተው ተግባራዊ ሊሆኑ በሚችሉ አሳቦች ዳብረው እንያቸው የምንለው። በዚህ ጉዳይ ካሁኑ ጠንክረን ከሠራን አምባገነኑ የመለስ ሥርዓት ከተወገደ በኃላ ያለስጋት ነገሮችን ልናስኬድ፣ ፍትህ እና የዜግነት እኩልነት ያለባት አዲሲቷን ኢትዮጵያን በቀላሉ ልንገነባ እንችላለን። ድር ቢያብር አንበሳ ያስር አይደል የሚባለው ከነተረቱ። አዎ እናብር!